የሲዖል ጥ ነዋሪዎች ብዙዎቹ ሴቶች ናቸው

 

ትርጉምና ቅንብር በአዘጋጁ

 

በእስልምና ውስጥ ወንዶችና ሴቶች በእስልምና እኩል ስላለመሆናቸው በጣም ግልፅ የሆነ መረጃን ለእኔ የሰጠኝ የሚከተለውና በሐዲት ውስጥ ያገኘሁት ጽሑፍ ነው፡፡ መሐመድም አለ፣ ‹‹የሲዖልን እሳት እንድመለከት ተደረግሁኝ በእሱም ውስጥ ያሉት ነዋሪዎቹ ‹ብዙዎቹ› ሴቶች ናቸው›› ይህ ዓረፍተ ነገር የተነገረው በሐዲት ውስጥ ሲሆን ሐዲቱም የሚገኘው በሚከተሉት ስብስቦች ውስጥ ነው፡-

ሳሂህ ቡካሪ 29፣ 304፣ 1052፣ 1462፣ 3241፣ 5197፣ 5198፣ 6449፣ 6546 (በፋተህ አል-ባሪ የቆጠራ ዘዴ)፡፡

ሳሂህ ሙስሊም፡ 80፣885፣ 907፣ 2737፣ 2738 (በአብድ አል-ባኪ የቆጠራ ዘዴ)፡፡

ሱናን አል-ታርሚዚ፡ 635፣ 2602፣ 2603፣ 2613 (በአህመድ ሻኪር የቆጠራ ዘዴ)፡፡

ሱናን አል-ናሳይ፡ 1493፣ 1575፣ (በአቢ ጉዳ የቆጠራ ዘዴ)፡፡

ሱናን ኢብን ማጃህ፡ 4003፣ (በአብድ አል-ባኪ የቆጠራ ዘዴ)፡፡

ሙስናድ አህመድ፡ 2087፣ 2706፣ 3364፣ 3376፣ 3559፣ 4009፣ 4027፣ 4111፣ 4140፣ 5321፣ 6574፣ 7891፣ 8645፣ 14386፣ 27567፣ 19336፣ 19351፣ 19415፣ 19425፣ 19480፣ 19484፣ 20743፣ 21729፣ 26508 (በኢህያ አል-ቱራዝ የቆጠራ ዘዴ)፡፡

ሙዋታ ማሊክ፡ 445 (ሙካታ ማሊክ የቆጠራ ዘዴ)፡፡

ሱናን አል-ዳሪሚ፡ 1007 (በአላሚ እና በዛርማሊ የቆጠራ ዘዴ)፡፡

ከዓመታት በፊት ስለእስልምና ምርምርን ሳደርግ ይህንን ሐዲት አንብቤዋለሁኝ፣ በእስልምናም ውስጥ ወንዶችና ሴቶች እኩል ስላለመሆናቸው ጠንካራ ማስረጃ ሆኖ አግኝቼዋለሁኝ፡፡ ይህንንም አባባሌን እንደሚከተለው ላብራራው፡- እንበልና በአንድ ትምህርት ቤት ሁለት ክፍሎች አሉ፣ ሁለቱም እኩል የሆኑ የተማሪዎች ቁጥር አላቸው፣ ቁጥሩም በጣም ብዙ ነው፡፡ ለሁለቱም ፈተና ሰጠናቸው እንበል፡፡ የክፍል (ሀ) ተማሪዎች ብዙዎቹ ፈተናውን ሲያልፉ የክፍል (ለ) ተማሪዎች ብዙዎቹ ደግሞ ወደቁ፡፡ ሁለቱም ክፍሎች አንድ ዓይነት የሆነ የአዕምሮ ችሎታ ቢኖራቸው፣ አንድ ዓይነት የትምህርት ደረጃ ቢኖራቸው፣ አንድ ዓይነት የሆነ ፈተና ቢሰጣቸው፣ የተቀራረበ ውጤት እንዲያገኙ አንድ ዓይነት ማበረታቻ ቢደረግላቸው፤ የክፍል (ለ) ተማሪዎች ለመውደቃቸው መልስ ሊሆን የሚችለው አንድ ትክክል ያልሆነ ነገር እንደተከናወነ ነው፡፡ ይህም ክፍል (ለ) እንደ ክፍል (ሀ) በሚገባ አልተማሩም ወይንም ደግሞ የክፍል (ለ) ፈተና በጣም ከባድ ነበር ማለት ነው ወ.ዘ.ተ፡፡ ስለዚህም ፈታኙ ሚዛናዊ ፈታኝ አልነበረም ማለት ነው፡፡

ከዚህ በላይ ያለው ምሳሌ ከላይ ለጠቀስነው ሐዲት ይሰራል፡፡ ወንዶችና ሴቶች እኩል ከሆኑ በሲዖልም ውስጥ ሊኖር የሚችለው የሴቶች ቁጥር ከወንዶች ጋር በአንፃራዊ መልኩ እኩል መሆን ይኖርበታል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ሊሆን የሚችለው ሴቶች ለኃጢአት የበለጠ የተጋለጡና በኃጢአትም በጣም የሚፈተኑ ናቸው (ከባዱ ፈተና) ወይንም ደግሞ ወንዶቹ ያላቸውን ተመሳሳይ እድል የላቸውም ማለት ነው (ደረጃው ዝቅ ያለ ትምህርት ነው ያገኙት)፡፡ ስለዚህም ይህ ደግሞ በስተመጨረሻው የሚያመለክተው ነገር እግዚአብሔር እነሱን በመፈተኑ ሚዛናዊ አልነበረም ማለት ነው ወይንም እነሱን ሲፈጥር ሚዛናዊ አልነበረም ማለት ነው፡፡

ከዚህ ላይ ልንጨምረው የምንችለው ነገር በተፈጥሮ እንደሚታየው ከሴቶች ይልቅ ብዙ ወንዶች ልጆች እንደሚወለዱ ነው (ከ5% በላይ) ማለትም በዚህ ምድር ውስጥ ከሴቶች ይልቅ በጣም ብዙ ወንዶች ኖረዋል (ምንም እንኳን ብዙዎቹ በወጣትነት ቢሞቱም) ስለዚህም (በምድር ላይ ከኖሩት ወንዶች ቁጥርም አንፃር እንኳን) ይህ ጉዳይ በጣም ጠንካራ ነው የሚሆነው፡፡

መሐመድ የተናገረው ነገር ምንም እንኳን ግልፅ ቢሆንም፣ ከእንግሊዝኛው ትርጉም ላይ ተቃውሞ ሊነሳ ይችል ይሆናል፡፡ ብዙዎች የሚለው ቃል በአረብኛ ትክክለኛ ትርጉሙ ምንድነው? 50.1% ከ 49.9% ተብሎ ሊተረጎም ይቻላልን? ወይንስ አረብኛው በቁጥር ላይ ከፍተኛ ልዩነት እንዳለ ያሳያል?

በአረብኛ ቃሉ ‹አክታር› የሚለው ሲሆን ብዙውን ጊዜ የሚያገለግለው በመጠን፣ በቁጥር፤ ወ.ዘ.ተ ላይ ትልቅ ልዩነት ሲኖር ነው፡፡ ስለዚህም ያ ሐዲት በሼኮች ሁሉ ዘንድ ግንዛቤ የተወሰደበት ‹እጅግ በጣም ብዙ› የሚል ትርጉምን እንደያዘ ነው፡፡ እኔም አንድ ጊዜ አንድ ሰው፡- ‹በሲዖል ውስጥ ካሉት ሰዎች ሁለት ሦስተኛዎቹ ሴቶች ናቸው› በማለት ሲናገር ሰምቻለሁ፡፡ በመሆኑም ከዓውዱ ስንነሳ 50.1% ከ 49.9% በማለት ለመተርጎም አይቻልም፡፡

ሌላው ምክንያት ደግሞ መሐመድ በዓይኑ ያየው እጅግ በጣም ትልቅ ልዩነት እንዳለ ነው፣ እርሱ ቆጠራን አላደረገም፣ እግዚአብሔርም ቁጥርን አልነገረውም፡፡ ስለዚህም ልዩነት ከታየ የ1% ወይንም የ2% ልዩነት ሊሆን በፍፁም አይችልም፡፡

በዚህ ጉዳይ ላይ እኔ ተጨማሪ ምርመራን አድርጌያለሁ፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ብዙ ጊዜ የሚመጣው ከዚህ በላይ ያየነው ሐዲት ነው፡፡ ሆኖም እንደሚከተለውም የሚልን ሌላ ሐዲት አግኝቻለሁ፣ በቡካሪ ላይ ‹የሲዖል ነዋሪዎች አብላጫው ሕዝብ ሴቶች ናቸው› የሚልን ነው፡፡ ለዚህ ያገለገለው የአረብኛው ሐረግ በጣም ግልጥ እንዳደረገው መሐመድ የሚያወራው ስለ እጅግ በጣም ብዙው የሲዖል ነዋሪ ሕዝብ ነው፡፡ Volume 7, Book 62, Number 124፡፡

ዑሳማ እንደተረከው፡-

ነቢዩ አለ፡- ‹እኔ ገነት በር ላይ ቆሜ ያየሁት በዚያ የሚገቡት ብዙዎቹ ሰዎች ድሆች እንደነበሩ ነው፣ ሃብታሞቹ በበሩ ላይ እንዲቆሙ ሲደረግ (ለሂሳብ ምርመራ)፤ ነገር ግን የእሳት ጓደኞች የሆኑት ወደ እሳቱ እንዲወሰዱ ይታዘዙ ነበር፡፡ ከዚያም እኔ በእሳቱ በር ላይ ቆምኩኝ እናም ያየሁት ወደዚያ የሚገቡት ብዙዎቹ ሴቶች እንደነበሩ ነው›፡፡ ይህ ሐዲት የሚገኘው፡-

ሳሂህ ቡካሪ፡ 5196፣ 6547 (ፋትህ አል-ቡካሪ የቆጠራ ዘዴ)፡፡

ሳሂህ ሙስሊም፡ 2736 (አብድ አል-ባኪ የቆጠራ ዘዴ)፡፡ እንዲሁም፤

ሙስናድ አህመድ፡ 21275፣ 21318 (ኢህያ አል-ቱራዝ የቆጠራ ዘዴ) ላይ ነው፡፡

ብዙ ለሚለው እዚህ በጥቅም ላይ የዋለው የአረብኛ ቃል 'Aammah (or 3ammah), ሲሆን ያለምንም ጥርጥር የሚያመለክተው (በአረብኛ) ‹እጅግ በጣም ብዙ› የሚለውን ነው፡፡ እንግዲህ ታያላችሁን? ስለዚህ ነው እኔ ‹ብዙ› የሚለው ብቻውን ጥሩ ትርጉም አይደለም የምለው፡፡ ከዚህ በላይ ለተጠቀሰው (Aammah) ለአብላጫው ሕዝብ ለሚለው ያገኘሁት የአረብኛ ትርጉም ነበር፡፡ ስለዚህም መሐመድ በትክክል ይናገር የነበረው ነገር በሲዖል ውስጥ ያሉት ሰዎች አብላጫዎቹ ሕዝብ ሴቶች ናቸው በማለት ነበር፡፡ ለዚህም ያሉት ምንጮች የሚከተሉት ናቸው፡-

በቡካሪ ውስጥ የሚገኙበት (የተጠቀሱበት) ቁጥር (በሁለቱም ሐዲቶች) 11 ጊዜ፡፡

በሙስሊም የተጠቀሱበት ጊዜ (በሁለቱም ሐዲቶች) 6 ጊዜ፡፡

በአህመድ የተጠቀሱበት ጊዜ (በሁለቱም ሐዲቶች)፡ 27 ጊዜ፡፡

በድምሩ የተጠቀሱበት ጊዜ (በዘጠኙም መጽሐፍት ሁሉ ባሉት ሁለቱም ሐዲቶች ውስጥ) 53 ጊዜ ነው፡፡

ይህ ‹በጣም ብዙዎቹ የሲዖል ነዋሪዎች ሕዝቦች ሴቶች ናቸው› የሚለው ሐዲት በብዙዎቹ ታማኝ መጻሕፍት ውስጥ በመጠቀሱ እና በሌሎችም የተያያዙ ተራኪዎች ውስጥ በመዘገቡ፣ በትክክል በነቢዩ የተባለ ነገር ነው፡፡ ስለዚህም ይህንን ሐዲት በመሰረታዊ ጠቃሚ አባባሉ ታማኝ ሊሆን አይችልም ብሎ ለማለት አይቻልም፡፡

የአዘጋጁ ማሳሰቢያ፡-

በእስልምና እምነት በሴቶችና በወንዶች መካከል ስላለው ግልፅ የሆነ ልዩነት ቁርአንም ሐዲትም ይመሰክራሉ፡፡ ሙስሊም ሴቶች ወደ ገነት እንደሚገቡ የሚጠቁም ምንም ዓይነት ቁርአናዊም ሆነ የሐዲቶች ማስረጃ የለም፡፡ ሲዖልን ያጣበቡት ሴቶች መሆናቸው በብዙ ቦታ በተመዘገበውና ከዚህ በላይ በተብራራው ሐዲት ውስጥ መነገሩ እጅግ በጣም አሰቃቂ ነው፡፡ አንድ ሃይማኖት ለሚከተሉት ሰዎች (ለወንዶችም ለሴቶችም) የሚሰጠው ተስፋ በእስልምና ለሴቶች አለመጠቀሱ ለምንድነው? ይህስ እውነታ ለወንዶች ለራሳቸው ምን ስሜት ይፈጥርባቸዋል? በእርግጥ እንደዚህ ዓይነቱ ፍትህ የጎደለው የፆታ ልዩነት ከእግዚአብሔር የመጣ ነውን? የዚህ ገፅ አዘጋጆች እነዚህንና ሌሎችንም ጥያቄዎች ሙስሊም ሴቶችም ሆኑ ወንዶች እንዲያስቡባቸው ይፈልጋሉ፡፡

የእግዚአብሔር ቃል መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተላልፈው መልእክት ግን አስደናቂ ነው፡፡ ማንኛውም የሰው ዘር ያለምንም የፆታ ልዩነት ኃጢአተኛ በመሆኑ የሲዖል ፍርድ የሚገባውና የሚጠብቀው ነው፡፡ አንድ ሰው በፆታው ወይንም በሃይማኖተኛነቱ፣ ወይንም በምድር ላይ በሰራው ጥሩ ስራ ከእግዚአብሔር ቅዱስ ፍርድ ሊድን አይችልም፡፡ የሰው ልጅ በሙሉ ያለምንም የፆታ ልዩነት በፍርድ ቁጣ ስር ነው፡፡ እንደዚህ ምንም ተስፋ ለሌለው የሰው ልጅ ፈጣሪው እግዚአብሔር የመዳኛና ከእርሱ ጋር የመታረቂያን ቅዱስና አስተማማኝ መንገድ አዘጋጅቷል፡፡ ይህም መንገድ ለኃጢአተኞች ሁሉ ምትክ በመሆን በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ለሕዝቡ ዋጋ በከፈለው በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለሚያምኑበት ሁሉ ተገልጧል፡፡

ያለምንም የፆታ፣ የዕድሜ እና የደረጃ ገደብና ልዩነት ኃጢአታቸውን ተናዝዘው ለኃጢአታቸው በሞተው በጌታ በኢየሱስ በኩል ባለው መታመን ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ሁሉ እግዚአብሔር እንደሚቀበላቸው ቃል ኪዳንን ገብቷል፡፡ አንባቢዎች ሆይ! በዚህ ቃል ኪዳን ውስጥ እናንተም ተጠቃሚ ልትሆኑና በክርስቶስ በኩል የዘላለምን ሕይወት በነፃ ልትወርሱና ገነትም ውስጥ ለዘላለም ከእግዚአብሔርና ከሕዝቡ ጋር ልትኖሩ ትችላላችሁ፡፡ ቀን የሚያመጣው ምን እንደሆነ አታውቁምና ይህንን እርምጃ ከመውሰድ እንዳትዘገዩ እንጋብዛችኋለን፣ ቸሩ እግዚአብሔርም በፀጋው ይርዳችሁ፣ አሜን፡፡

 

የትርጉም ምንጭ: The Majority in Hell are Women

ለእስልምና መልስ አማርኛ  ዋናው ገጽ